Sunday, September 22, 2024
spot_img

አቶ ዳውድ ኢብሳ ላለፈው አንድ ወር በቁም እስር ላይ እንደሚገኙ የኦነግ ጊዜያዊ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ነግረውኛል ብሎ አዲስ ስታንዳርድ አስነብቧል

Update: አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ ሚያዝያ 26፣ 2013 ― አቶ ዳውድ ኢብሳ ላለፈው አንድ ወር በቁም እስር ላይ እንደሚገኙ የኦነግ ጊዜያዊ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ነግረውኛል ብሎ አዲስ ስታንዳርድ አስነብቧል፡፡

እንደ ሕዝብ ግንኙነቱ ከሆነ የኦነግ ሊቀመንበሩ አቶ ዳውድ ኢብሳ ከመጋቢት 24 አንስቶ በቤታቸው በቁም እስር ላይ ይገኛሉ፡፡

ኃላፊው አክለውም በእለቱ የአቶ ዳውድ ጠባቂዎችም በጸጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ስር መዋላቸውን አስታውሰው፣ በእለቱ የተያዙት ጠባቂዎቻቸው መካከል ለሁለት ሳምንታት በንፋስ ስልክ ላፍቶ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው የተለቀቁ መኖራቸውን እንዲሁም፣ ሌሎች ሁለት ደግሞ አሁንም በቡራዩ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው ይገኛሉ ብለዋል፡፡

በዘገባው ሥማቸው ያልተጠቀሰው የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ትላንት ምሽት በኦሮሞ ነጻነት ግንባር ሊቀመንበር አቶ ዳውድ ኢብሳ መኖሪያ ቤት አካባቢ ተፈጥሯል ስለተባለውም ጉዳይ አንስተዋል፡፡

እንደ ሕዝብ ግንኙነቱ ከሆነ ምሽቱን ከሦስት እስከ አራት ሰአት ባለው ጊዜ የታጠቁ የጸጥታ ኃይሎች የሊቀመንበሩን ቤት ጠባቂዎች ጥሰው ለመግባት ሙከራ አድርገዋል፡፡

ክስተቱን ተከትሎም እነዚሁ በሦስት መኪኖች መጥተዋል ያሏቸው የጸጥታ አካላት በአካባቢው ተሰብስበው የነበሩ ወጣቶችን መምታታቸውን እንዲሁም ሌሎችን ማሰራቸውንም ገልጸዋል፡፡

በሕዝብ ግንኙነቱ በትክክል እነማን እንደሆነ ያልተጠቀሱት የጸጥታ አካላት በሊቀመንበሩ መኖሪያ ቤት ውስጥ የሚገኙ ስልክ እና ኮምፒውተሮችን መውሰዳቸውን የተነገሩ ሲሆን፣ የአቶ ዳውድ አሁናዊ ሁኔታም በትክክል አይታወቅም ነው የሚሉት፡፡

አዲስ ስታንዳርድ በጉዳዩ ላይ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶክተር ዳንኤል በቀለን አናግሬ ስለ ትላንት ምሽቱ ክስተት የሰሙት ነገር ባይኖርም፣ የቁም እስሩን በሚመለከት ግን መረጃውን በቅርበት እየተከታተሉት እንደሚገኙ ነግረውኛል ብሏል፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img