Sunday, October 6, 2024
spot_img

የዋጋ ንረትን ለመቅረፍ ‹‹የተጠኑ ርምጃዎች›› እየተወሰዱ እንደሚገኑ የብሔራዊ የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ አሳወቀ

አምባ ዲጂታል፣ ዐርብ ሚያዝያ 22፣ 2013 ― ኮሚቴው ዛሬ ባወጣው መግለጫው በአገሪቱ የመጣውን የፖለቲካ ለውጥ ተከትሎ ተከናውነዋል ያላቸውን ከኢኮኖሚ ጋር የተገናኙ ሥራዎች አንስቷል፡፡

‹‹ከለውጡ የኢኮኖሚው ችግሮችን ለማረም ባደረግነው ከፍተኛ ጥረት አብዛኛው የዓለም የኢኮኖሚ ዕድገት ከዜሮ በታች በሆነበት ጊዜ፣ የሀገራችን ኢኮኖሚ አሉታዊ ተጽዕኖዎችን በመቋቋም አዎንታዊ ዕድገት ለማስመዝገብ ችሏል›› ያለው ኮሚቴው፣ ያም ሆኖ የተለያዩ ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ችግሮች በኢኮኖሚው ላይ ጫና ሳይፈጥርበት እንዳላለፈ በመጠቆም፣. በተለያዩ የመፍትሔ አማራጮች ተጽዕኖችን ለማጥፋት ቢሞከርም ‹‹ሙሉ በሙሉ ማስቀረት አልተቻለም›› ሲል ሁኔታውን አስረድቷል፡፡

ኮሚቴው በመግለጫው ከተጽዕኖዖቹ አንዱ ነው ያለው የዋጋ ንረትን ነው፡፡ ‹የዋጋ ንረት ለረጅም ጊዜ የሀገራችን ኢኮኖሚ ችግር ሆኖ ቆይቷል በማለትም፣ ገጥመዋል ያላቸው ‹‹ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ፈተናዎችን›› ተቋቁሞ የኑሮ ውድነት ሕዝቡን አደጋ ላይ እንዳይጥለው ለማድረግ፣ ፈተናዎቹ ከተከሠቱባቸው ቀናት ጀምሮ ‹‹አስፈላጊዎቹን ርምጃዎች ሁሉ›› ሲወሰዱ ቆይቷል ብሏል፡፡

‹‹ሆኖም ችግሩ ከሀገራዊና ከዓለም አቀፍ ችግሮች ጋር የተገናኘ በመሆኑ ችግሩን ተቆጣጥረን ለመቆየት ያደረግነው ጥረት የምንፈልገውን ያከል ውጤታማ ሆኖ አልተገኘም›› ያለ ሲሆን፣ ‹‹ይህም በሕዝባችን ኑሮ ላይ የፈጠረውን እክልና አደጋ በመረዳት የኑሮ ውድነቱን ሊቀርፉ የሚችሉ ርምጃዎችን በተጠና መንገድ መውስድ ጀምረናል›› በማለት አዳዲስ ማስተካከያ መንገዶች ላይ እየሠራ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡

የብሔራዊ የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴው እየተወሰዱ ነው ካላቸው የማሻሻያ ርምጃዎች መካከል ‹‹የግል ባለ ሀብቱ መሠረታዊ ሸቀጦችን በቀላሉ ወደ ሀገር እንዲያስገባ›› የሚለው እንደሚገኝበት ነው ያሳወቀው፡፡

አክሎም ‹‹መንግሥት በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የወሰዳቸውና አየወሰዳቸው ያሉ ርምጃዎች ኢኮኖሚውን ከነበረበት ችግር ውስጥ አውጥተው ወደ ፊት የሚያስፈነጥሩና የኢትዮጵያን ብልጽግና የሚያረጋግጡ እገደሚሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም›› ያለው ኮሚቴው፣ ሆኖም አገሪቱ ‹‹ከውጭም ከውስጥም በጠላቶች በተወጠረችበት በዚህ ጊዜ ችግሮቻችንን ለመፍታት በአንድ ላይ መቆምና መተባበር›› አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝቧል፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img