አምባ ዲጂታል፤ ቅዳሜ መጋቢት 2፣ 2015 – የፌስቡክ ባለቤት የሆነው ሜታ ኩባንያ ሌላኛውን የማኅበራዊ ትስስር መድረክ ትዊተርን የሚቀናቀን መድረክ እያበለጸገ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡
ሜታ ትላንት ዐርብ እንዳስታወቀው፤ ኩባንያው እየሠራበት የሚገኘው አዲሱ የማኅበራዊ ትስስር መድረክ የጽሑፍ ማስታወሻዎችን ለማጋራት የሚውል ነው፡፡
የማርክ ዙከርበርግ ሜታ ኩባንያ ከፌስቡክ በተጨማሪ ኢንስታግራም እና ዋትስአፕን በሰሩ እንደሚያስተዳድር ይታወቃል፡፡
ሜታ አሁን እቀናቀነዋለሁ የሚለው ትዊተር ባለፈው የፈረንጆቹ ዓመት በኤሌክትሪክ መኪና አምራቹ ቴስላ ባለቤት ኤሎን መስክ እጅ መግበቱ ይታወቃል፡፡
ከዓለማችን ግንባር ቀደም ቱጃሮች መካከል አንዱ የሆነው መስክ ትዊተርን በ44 ቢሊዮን ዶላር ከገዛ በኋላ በማኅበራዊ ሚዲያው አጠቃቀም ዙሪያ እያስተዋወቃቸው ባላቸው ፖሊሲዎች ትችት ሲቀርብበት ቆይቷል፡፡